በዚህም ዕለት በዓለም አቀፍ ደረጃ የኢንቨስትመንት ስኬታቸውን የምናበስርበት፣ ለሀገር ልማት ያበረከቱት ሰፊ አስተዋጽኦ የሚወደስበት፣ የወገን አለኝታነታቸውን እውነተኛ ምሥክርነት የምንዘክርበት ዕለት ነው ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በዘመናዊ ማኔጅመንት ሥርዓት ውስጥ እንድንመራ አብሮ አደጋቸውንና ልዩ የመሪነት ችሎታ ያላቸውን ዶ/ር አረጋ ይርዳውን በቺፍ ኤግዚኪዩቲቭ ኦፊሰርነት ለሚድሮክ ኢትዮጵያ መስጠታቸውን የምናመሰግንበት፣ እንዲሁም በየዓመቱ የሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ኩባንያዎች ሠራተኞች ከቤተሰቦቻችን ጋር በመሆን ይህንን በዓል ስናስብ ለሊቀመንበራችን ረጅም እድሜ እንዲሰጥልን በየእምነታችን የምንማፀንበት ዕለት ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ በማለት አብራርተዋል፡፡
“የሚድሮክ ኢትዮጵያ ሊቀመንበርና ባለቤት የሆኑት ሼክ ሙሐመድ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ በዓለም እና በልዩ ሁኔታም በኢትዮጵያ እያካሂዱ ያሉት ኢንቨስትመንት በቀጥታ ተጠቃሚ የሆነውን የኩባንያዎቹን ሠራተኞች ብቻ ሳይሆን እያንዳንዱን ለሀገር እድገት የሚቆረቆር ዜጋን ልብ በኩራት ይሞላል፡፡ በግሉ የኢንቬስትመንት ዘርፍ በሀገራችን ከፍተኛ ቁጥር ያለውን ሠራተኛ አቅፎ የሚገኘው የሚድሮክ ኢትዮጵያ ኢንቬስትመንት ሲሆን የሊቀመንበራችን የልደት ቀን ዓመታዊ በዓል በመሆን ማክበር ከጀመርን አራት ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ በዚህም ዕለት መላው ሠራተኛና ቤተሰቡ እንኳን ለልደት በዓላቸው በሰላም አደረሳቸው የሚለውን የሠራተኞች መልዕክት ዶ/ር አረጋ ይርዳው እንዲያደርሱልን ስጠይቅ በታላቅ አክብሮት ነው፡፡” ብለዋል፡፡ በዕለቱ በተካሄደው ፕሮግራም በሲ.ኢ.ኦ ቢሮ የሥራ ኃላፊዎች የሆኑት አቶ ለገሰ ተ/ማርያም የፋይናንስና ማቴሪያልስ ማኔጅመንት አገልግሎት ኃላፊና ወ/ት ዕፀሕይወት ድንቁ የማርኬቲንግ ሴልስና ቢዝነስ ዲቨሎፕመንት አገልግሎት ኃላፊ በየበኩላቸው ባደረጉዋቸው ንግግሮች የሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ኩባንያዎች እያደረጉ ያሉትን እንቅስቃሴና ያሳዩዋቸውን እድገቶች በዝርዝር አስረድተዋል፡፡ በዚህ ገለፃ መሠረት ከስምንት ዓመታት በፊት አምስት የነበረው የኩባንያዎቹ ቁጥር በአሁኑ ወቅት 15 የደረሰ ሲሆን፤ የሠራተኛ ብዛት ከ5500 በላይ በመድረስ የ30 ከመቶ እድገት አሳይቷል፡፡ ዓመታዊ የደመወዝ ክፍያው ከብር 33.6 ሚሊዮን ወደ 64.3 ሚሊዮን ያደገ ሲሆን የ90 ከመቶ እድገት አሳይቷል፡፡ ሽያጩም ከ491.8 ሚሊዮን ወደ ብር 1.36 ቢሊዮን በማደግ በ175 ከመቶ እድገት አሳይቷል፡፡ ቀደም ሲል የመነሻው ኢንቬስትመንት ብር 3.77 ቢሊዮን የነበረ ሲሆን፤ በዚህ የስምንት ዓመታት ጊዜ በተጨማሪ ብር 1.09 ቢሊዮን ኢንቬስት ተደርጓል፡፡ ይህም አጠቃላዩን ኢንቬስትመንት ወደ ብር 4.86 ቢሊዮን ያደርሰዋል፡፡